30/12/2023
ብልግናን መገለጫችን ባናደርግስ?
"ቤቲዬ የወሰንሽውን ውሳኔ እቃወማለሁ" እያሉ የሚያለቅሱ አባት ቪድዮ እዚህ መንደር ሲዘዋወር ቪድዮው ላይ ባለው ቲክቶክ አካውንታቸው ፈልጌ አገኘኋቸው። እሳቸው duet ያደረጉበትን ቤተልሄም ግርማ የምትባል እህት ቪድዮም ገብቼ አየሁት ። ልጅቷ ከዚህ በፊት በቲክቶክ ላይቭ እየገባች ለተለያዩ ታማሚ ወገኖች ገቢ ማሰባሰብ ስትሰራ የቆየች እህት ነች። እሷ ባሰባሰበችው ብር ብዙዎች ታክመው ድነዋል መድሀኒያለም ይስጣት። መጨረሻ ላይ በለቀቀችው ቪድዮ ግን እያለቀሰች በግልፅ ምክንያቱን መናገር ባትፈልግም "ከዚህ በኋላ በቲክቶክ የማደርገው እንቅስቃሴ በቃኝ" ብላለች። ስሜታዊ ያረጋትና ሞራሏን የነካው የመንደሩ ሰዎች ስድብና ጋጠወጥነት ይመስለኛል። ስርአተ ማህበራችን መልካሞችን የሚሰብር ባለጌን የሚያገን እየሆነ መጥቷል።
እኝህ አባት ቀድሞ በሷ እርዳታ ቤተሰባቸውን ያተረፉ ናቸው አለያም ደግሞ በመልካም ተግባሯ የሚደሰቱ ናቸው። አሁን በሞራሏ መሰበር አዝነው "እባክሽ መልካም ተግባርሽን አታቁሚ" እያሉ አለቀሱ። ጥቂት ማጣራትም የማያረጉ የዚህ መንደር ባለጌዎች ደግሞ የሳቸውን ቪድዮ ብቻ አምጥተው በመለጠፍ "ቤቲ የምትባል ሴት አፍቅሮ ሲያለቅስ" በማለት መዘባበቻ አድርገዋቸዋል። በተለይም ያሣፈረኝ ይኼን ቪድዮ ከለጠፉት ውስጥ ብዙዎቹ ሴቶች መሆናቸው ነው።
እኝህ አባት የቴክኖሎጂውን አደገኛ መልክ አልተረዱት ይሆናል በቀናነት ስሜታቸውን ገለፁ። እንዲ መዘባበቻ ስታደርጓቸው ግን ቤተሰብ ፣ ስብእና ና ልጆች እንዳላቸው ራሱ ማስተዋል አቅቷችኋል።
በአባታችሁ ላይ እንዲህ ቢደረግ እንዲህ የመሣቅ ሞራል አላችሁ ይሆን ?
Tesfa.G.neda