09/08/2025
የመንግሥት ሰራተኞች የደረጃ እድገት እና የእርከን ጭማሪ በአዲሱ ረቂቅ አዋጅ ተፈቅዷል! - የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን❗
አዲሱ የፌዴራል መንግስት ረቂቅ የሰራተኞች አዋጅ ሰራተኞች ተመዝነው በአፈጻጸማቸው የሚለዩበት እንደሆነ የፌደራል ሲቪል ሰርቪስ ኮሚሽን ኮሚሽነር መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) ገለጹ።
አዋጁን በተዛባ መንገድ መረዳት አይገባም ያሉት ኮሚሽነሩ፤ አንድ ሰራተኛ ሁለት ጊዜ ተመዝኖ ውጤቱ ከመካከለኛ በታች ከሆነ ከስራው እንደሚሰናበትም ጠቁመዋል።
በዚህ ምዘና በቂ ውጤት ያመጡ ሰራተኞች ደግሞ የደረጃ እድገት እንዲሁም በየሁለት ዓመቱ የሚኖር የእርከን ጭማሪ እንዲያገኙ በአዋጁ ተደንግጓል ብለዋል።
የአዋጁ ዋና ዓላማ ሰራተኛን መቀነስ ሳይሆን ማብቃት ነው ያሉት መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር)፤ በምዘናው ደረጃ አሟልተው ብቁ የሆኑ፣ የተወሰነ ክፍተት ያለባቸው እና ሰፋ ያለ ክፍተት የታየባቸው ተለይተው ክፍተቶቹ በስልጠና እየተሟሉ ሶስቱም በመንግሥት መዋቅር ውስጥ የሚቀጥሉ ናቸው ብለዋል።
የመንግሥት ሰራተኛው በስራው ተመጣጣኝ ገቢ አለማግኘቱ በኑሮው ላይ ጫና ፈጥሮበታል፤ አዋጁ ይህን ችግር ለመፍታት የሚያስችል ነው ወይ ተብሎ ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ማብራሪያ፥ አዋጁ የብቃት ምዘናውን ያለፉና መስፈርቱን የሚያሟሉ ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪ በእርከንና በደረጃ ዕድገት እያገኙ የሚሄዱበትን አስገዳጅ አሰራር መደንገጉን ተናግረዋል።
አዋጁ የፐብሊክ ሰርቪስ አገልግሎትን ለማሻሻልና ዲጅታል ሲቪል ሰርቪስን ለመፍጠር ዓላማ ያደረገ ነው ያሉት ኮሚሽነሩ፤ ሁሉም ብሄረሰብ የተማረ የሰው ኃይል አለው ተብሎ ስለሚታሰብ ብዝሃነትን መሰረት ያደረገ ፐብሊክ ሰርቪስ ለመገንባት መታሰቡን ተናግረዋል።
ሥራ ላይ ያለው የፌዴራል መንግሥት የሰራተኞች አዋጅ ፖሊሲን መሰረት አድርጎ የተቀረጸ አይደለም ያሉት ኮሚሽነሩ፤ የመንግሥት አገልግሎትን መሰረታዊ በሆነ መልኩ ለመቀየር የሚያስችልም አልነበረም ብለዋል።
አሁን የተዘጋጀው አዋጅ ነጻና ገለልተኛ ሲቪል ሰርቪስ ለመገንባት፣ የሰራተኛውን ለማረጋገጥ፣ ብዘሃነትና አካታችነትን በተገቢው መንገድ ለመምራት እንደሚረዳ መኩሪያ ኃይሌ (ዶ/ር) ገልጸዋል።
Reposted❗❗
ምንጭ ከዳዊት ገብረእግዚአብሔር ❗
Omotic South Ethiopia ገጻችንን follow በማድረግ አዳድሰና ወቅታዊ መረጃ ያግኙ ❗