07/10/2022
የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠር ነዋሪዎችን የመብራት ተጠቃሚ ያደረገው የቦረናው ታዳጊ 200 ሺህ ብር ተሸለመ
ከተለያዩ ቁሶች የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠር የአካባቢውን ነዋሪዎች የመብራት ተጠቃሚ ያደረገው የቦረናው ታዳጊ አዳን ሁሴን ከኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር አቶ ሽመልስ አብዲሳ እጅ የ200 ሺህ ብር ሽልማት ተቀብሏል።
በቦረና ዞን ዋጪሌ ወረዳ ዌብ ከተማ የሚኖረው የ15 ዓመቱ የ8ኛ ክፍል ተማሪ አዳን ሁሴን ዲዳ ከተለያዩ ቁሶች የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠር የሚማርበትን ትምህርት ቤት እና የአካባቢውን ነዋሪዎች የመብራት ተጠቃሚ አድርጓል።
በፈጠራ ሥራዎቹ የኤሌክትሪክ ኃይል ከመፍጠሩ አስቀድሞ የተለያዩ ነገሮችን በመፍጠር የሚታወቅ ባለ ልዩ ተሰጥኦ ታዳጊ መሆኑንም በአካባቢው የሚያውቁት ሁሉ ይናገራሉ።
ከፈጠራ ሥራዎቹ መካከል የተለያዩ ቁሶችን በመጠቀም የኤሌክትሪክ ኃይል በመፍጠሩ ከሚማርበት ቱላ ዌብ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በተጨማሪ በዌብ ከተማ 37 መኖሪያ ቤቶች መብራት እንዲያገኙ አድርጓል።
ሽልማቱን ያበረከቱት አቶ ሽመልስ አብዲሳ፣ “እንደ ተማሪ አዳን ሁሴን ያሉ ሰዎች ሲበዙ በሀገር ዕድገት ውስጥ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ይኖራቸዋል” ብለዋል።
የኦሮሚያ ክልል መንግሥት እንደዚህ ዓይነት የፈጠራ ክህሎት ያላቸውን ታዳጊዎች በዘላቂነት ለመደገፍ ቁርጠኛ መሆኑን የክልሉ የኮሙዩኒኬሽን ቢሮ መረጃ አመልክቷል።