27/02/2021
Some psychology— ለቅዳሜ።
እቴሜቴ
--
ጋሼ Abera Lemma በእውነተኛ ገጠመኛቸው ላይ ተመስርተው የሰሩት ስራ ነበር— እቴሜቴ። በማለዳ ስንቅ የግጥምና የልብወለዶች ስብስብ ውስጥ ተካቶ ይገኛል። የአጭር አጭር የሚባል አይነት ልብወለዳዊ ስራ ነው። 1978 ላይ የተፃፈ።
አንደኛ መደብ አንፃርን በመጠቀም ተራኪው ገፀባህርይ "እቴሜቴ" እያለ የሚጠራትን አክስቱን ለመጠየቅ በሄደበት የገጠመውን ይተርካል።
አክስቱ ራሷን ከማህበራዊ ስርአት ያገለለች ፣ ማህበራዊ ስርአቱም ያገለላት ምስኪን ሰው መሆኗን እናነባለን። ባሏን በሞት እንደተነጠቀች ቀጥሎም ልጇ በስደት ወደ አሜሪካን በመራቁ ብቸኝነት ያጠቃት ነበረች።
ባሏን በሞት ባጣችበት በአንደኛው ወቅት ከባል ቤተሰብ የደረሰባትን ማህበራዊ ጉንተላ እንደቀልድ አልወሰደችውም። ከፍተኛ ቂም አስቋጥሯት ኖሯል።
በባሏ ቀብር ላይ የሟች እህት በአደገኛ ምፅት እንዲህ ስትል ሙሾ ታወርዳለች።
"ለኛ ይብላኝ እንጂ ለእህት ወንድሞቹ
እሷስ ታገባለች ከባልንጀሮቹ "
ታዲያ የሟች ሚስት ከሃዘኑ ጋር የደረሰባት የጎሚ ሙሾ ስሜቷን ነክቶት ምላሽ ታበጃለች።
"እንዴት ያለሽ ሴት ነሽ ግፍን ተናጋሪ
አንቺም ባልሽ ሞቶ እንደኔ ተዳሪ! "
ከዚህ በኋላ የባል ቤተሰብ ጋር የነበራት ነገር እንዳከተመ በወፍ በረር እናነባለን(የአጭር አጭር ልብወለድ ዋና ባህሪይ ጥድፊያ መሆኑን ልብ ይሏል)።
በታሪኩ ባልተገለፀ ሁኔታ ብችኛ ልጇን በሞት እንዳጣችም ከታሪኩ እንረዳለን።
ከዚህ በኋላ "እቴሜቴ" ራሷ ላይ ዘጋች። ከፍተኛ የሆነ ጥላቻ፣ ጥርጣሬና ፍርሃት ወርሷት ከቤት መውጣት ታቆማለች። ዶሮዎችዋ ሳይቀሩ ከቤት እንዳይወጡ በማድረጓ የፀሃይ ብርሃን አይተው አያውቁምና ላባቸው ከቆዳቸው ላይ ረግፎና ከስተው እንደሚታዩ ተራኪው ገፀባርይ ይነግረናል።
ተራኪው ገፀባህርይ አክስቱን ለማግኘት ሄዶ ሳይሳካለት ረጅም ሰአት በሩን እንድትከፍት ደጅ ሲጠና እናነባለን። አድፍጣ ጠብቃ የቤቱን በር ከመክፈቷ በፊት የሰካካቻቸውን ውታፎች በማንሳት ሽንቁሮችን ለመክፈት ስትሞክር እያያት ግራ ይጋባ ነበር።
ሌሎች በሙሉ በሷ ላይ እንደተነሱና ጠላት እንደሆኗት በማመኗ ፍርሃት ውስጥ ነበረች። ከቤቷ ውጪ ያለው ሁሉ ጠላቷ እንደሆነ ታስባለች። እያንዳንዱ የጎረቤቶችዋ ግብሮች በሙሉ እሷን ለማጥቃት የሚፈፀሙ እየመሰላት አፀፋ ካልመለስኩ እያለች ራሷን ታሰቃያለች።
በሩን ከከፈተችለት በኋላ የጠየቀችው ፣ በሌላም አውድ ደጋገማ የምትጠይቀው መሰረታዊ ጥያቄ አለ።
"ንፁህ ነህ አይደል? "
ታሪኩን እናንተ ጨርሱት። ደራሲውን ምን ለማንሳትና ለማሳየት ፈለጉ?
ጥቂት ሥነልቡና እናክልበት።
በመጀመሪያ በ70ዎቹ ውስጥ ከተፃፉ ሥነልቡናዊ ይዘት ያላቸው ስራዎች ተጠቃሽ መሆን የሚችል ልብወለድ ነው። ጋሼ አበራን ሞርቪየር "በጥቋቁር አናብስት" መፅሃፉ ኤክስፐርሜንታል ደራሲ መሆናቸውን ሲገልፅ ምክኒያት ነበረው። የተለመደውን የ70ዎቹ ይዘት፣ ጭብጥና የአፃፃፍ ቴክኒክ ለመነጠል ያደረጉትን ሙከራ ስላጤነ ነው።
በታሪኩ የተንፀባረቀው ሃሳብ በማህበረሰባችን እጅግ የተለመደ እና ቦታ የማንሰጠው ነገር ግን የብዙ ጎጆዎችን ጤናማ ማህበራዊ መስተጋብር ያፈረሰ ስነልቡናዊ ችግር ነው።
Paranoid Personality Disorder (PPD) ይባላል። ያለ በቂ ምክኒያት ጣራ የነካ ጥርጣሬ ፣ ያለማመን እና ሌሎችን በጠላትነት የመሳል አባዜ ነው። የሥነአዕምሮ ቀውስ ሆኖ ይታወቃል።
በጎርምስና እድሜ ወይም በወጣትነት እድሜ ሊጀምር ይችላል።
በምን እንደሚከሰት ሳይንስ የጠራና ውል ያለው መንሥኤ አላበጀም ነገር ግን ሥነሕይወታዊና ሥነልቡናዊ መላምቶች አሉ።
ሥነሕይወታዊው መላምት ከጄነቲክስ ጋር ይያያዛል። ስኪዞፍሬኒክ ጋር የተያያዘ የስነአዕምሮ ቀውስ የነበረበት ቤተሰብ ጋር የሚዛመድ እና ተያይዞ በዘር ሊመጣ እንደሚችል ይገመታል።
ሥነልቡናዊ መላምቶች ደግሞ የልጅነት ጊዜ አንዳች የህይወት አጋጣሚዎች ፣ ልቡናን የሚያኮማትር ሃዘን እና ማህበራዊ ግፊቶች በተናጥል ወይም ተዳምረው PPD ን እንደሚከስቱ ይገመታል።
በዚህ የአዕምሮ ቀውስ የተጠቁ ግለሰቦች ከብዙ በጥቂቱ የሚከተሉት ባህሪያትን ያሳያሉ።
• ከፍተኛ የሆነ ሰዎችን ያለማመን፣ የመጠራጠር ዘንባሌ ሲኖራቸው በዚህ የተነሳ ማህበረሰቡን ፈፅሞ ይጠሉታል፣ ራሳቸውን ያገላሉ።
• በዙሪያቸው ያለው ሁሉ ጠላታቸው ይመስላቸዋል
• ሁሌም በነሱ ላይ የሚነሳሳ እንዳለና አደጋ እንደተጋረጠባቸው ይሰማቸዋል
• ቂም ይይዛሉ። ፈልሞ ለይቅርታ ዝግጁ አይደሉም
• የተቀረው ማህበረሰብ "ውስጣዊ ንፅህና" እንደሌለው ሲሰማቸው የገዛ ራሳቸው ደግሞ ሁሌም ልክ ነው በሚል ያምናሉ።
• ቁጡና ጠብጫሪዎች ሊሆኑ ይችላሉ
• ረፍት አልባና ውስጣዊ ውጥረትን ለማርገብ አልታደሉም… ወዘተ…
እነዚህን ባህሪያት ይዘን ከላይ የተነሳው ታሪክ ውስጥ ገፀባህሪዋ ለPPD እንደተጋለጠች እንገምታለን።
መነሾውም ሥነልቡናዊ መላምቶች በሚል ያስቀመጥናቸው ከፍተኛ ሃዘን እና ማህበረሰቡ ማንነታቸን የሚቀበልበት መንገድ እንደሆነ ከአጭር ታሪኳ ተነስተን የግል መላምት እናስቀምጣለን።
ገፀባህሪዋ በደረሰባት ሃዘን እና ሃዘኗን በማስታመም ሂደት ላይ የነበረው የማህበረሰቡ በቁስል ላይ "እንጨት የመስደድ አባዜ" ለአዕምሮ ጤና እክል ዳርጓት አለምን ተሸሽጋት ትውላለች።
PPD በሳይኮ ቴራፒ መንገዶች / cognitive therapy የህክምና መንገድ ሊቀረፍ ይችላል(ታዲያ ሁሌም ላይሳካ እንደሚችል ይታመናል)። ካልታከመና ካልተቀረፈ ደግሞ ከቀላል አንስቶ የቀን ተቀን አውድን ለመከወን የሚያስቸግር ሁኔታ ላይ የሚያደርስ ውስብስብ የጤና ቀውስ ይሆናል። ተጠቂው በራሱም ሆነ በማህበረሰቡ ላይ ጉዳት ሊያደስ ጭምር ይችላል።
በኛ ሃገር ህክምናው አልዳበረም። ትኩረት የሚሰጠው ነገር ሆኖ አይታይም። እንጂ በየቤቱ ከላይ በልብወለዱ የተሳችዋ አይነት ይኖራሉ።
ማህበረሰቡ የዚህ አይነት ሰዎችን የሚረዳበትን መንገድ መለስ ብሎ በመቃኘት ማህበራዊ ዕምነትና መተሳሰሰብን ለዚህ አይነት ጉዳተኞች በማሰየት "በአለማመንና በጥርጣሬ የታወከ ልባቸውን" የሚያክምበት የራሱ የሆነ መንገድ እንደየባህሉ ስለማይጠፋ ያንን በማድረግ "እብድ " ብሎ ከማግለል ከፍ ማለት ይኖርበታል።