12/11/2019
የብሔራዊ ስታዲየም የሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ ከ10 ቀናት በኋላ ይጀመራል-የኢፌዴሪ ስፖርት ኮሚሽን
*****************
በ2 ነጥብ 47 ቢሊዮን ብር ወጪ ህዳር 2008 ዓ.ም የተጀመረው የብሔራዊ ስታዲየም የሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ ከአስር ቀናት በኋላ እንደሚጀመር የኢፌዴሪ ስፖርት ኮሚሽን አስታውቋል፡፡
ከ62 ሺህ በላይ ተመልካቾች የሚይዘው ይህ ስታዲየም የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ 99 በመቶ መጠናቀቁ ይታወሳል፡፡
ስታዲየሙ ግንባታ ሲጀመር ከተያዘው ጊዜ ውጭ ተጨማሪ ስድስት ወራት ወስዶ አሁን 99 በመቶ ደርሷል ሲሉ የኢፌዴሪ ስፖርት ኮሚሽን የኮሚኒኬሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ናስር ለገሰ በተለይ ለኢቲቪ ገልጸዋል።
በቻይና ስቴት ኮንስትራክሽን ኢንጅነሪንግ ኮርፖሬሽን አማካኝነት እየተገነባ ያለው ፕሮጀክቱ 2 ቢሊዮን ብር ክፍያ ለመጀመሪያው ምእራፍ ግንባታ መፈጸሙን ኃላፊው ተናግረዋል።
እንደ አቶ ናስር ገለፃ፣ ከውጪ የሚገቡ እቃዎች መዘግየት፣ የብረት ዋጋ መናር ፣የውጭ ምንዛሪ እጥረት እንዲሁም ወቅታዊ የሀገሪቱ ሁኔታ የስታዲየሙ የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ ይጠናቀቃል ከተባለበት ጊዜ ተጨማሪ ስድስት ወር አስፈልጎታል።
የአደይ አበባ ስታዲየም የሁለተኛው ምዕራፍ ግንባታ የጨረታ ሂደት 11 ወራትን ፈጅቷል ያሉት አቶ ናስር ጨረታው ሶስት ጊዜ ወጥቶ በመጨረሻ አሁን ላይ ስምምነት ተደርሷል ብለዋል።
በመጪዎቹ 10 ቀናት ውስጥ ጨረታውን ያሸነፈው ድርጅት ይፋ ተደርጎ ወደ ስራ እንደሚገባም ነው የገለፁት፡፡
የስታዲየሙ ምእራፍ 2 ግንባታ የጣራ ስራ፣ የወንበር ገጠማ፣ የፊኒሺንግ፣ የሴኩሪቲ፣ የተለያዩ መሰረተ ልማት የማሟላት ስራዎች እንዲሁም ፓርኪንግ፣ የዋና ገንዳ እና ጂምናዚየም ስራዎች ተካተውበታል።
ስታዲየሙ ለተለያዩ ሀገራዊ፣ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፋዊ ኩነቶችን እንዲያስተናግድ 60,000 መቀመጫዎች እንዲኖረው ተደርጐ እየተገነባ ሲሆን ለከፍተኛ አመራሮች ፣ ለሚዲያ፣ ለስፖርተኞች፣ ለዳኞች እና ለክብር እንግዶች 2,000 ተጨማሪ መቀመጫዎች ስለሚሰሩ ብሔራዊ ስታዲየም 62,000 ተመልካቾች በድምሩ ማስተናገድ ይችላል ተብሏል።
ከስታዲየሙ ውጭ 3,231 ተመልካች ማስተናገድ የሚችሉ ትናንሽ የእግር ኳስ ሜዳዎች እና የመሮጫ መም የሚኖረው ሲሆን 3,500 መኪናችን የማስተናገድ አቅም አለው።
የሂሊኮፕተር ማረፊያ፣ የቮሊቮል፣ የቅርጫት ኳስ፣ የባድሜንተን፣ የሜዳ ቴኒስ፣ አምፊቲያትር አዳራሾች፣ ሰው ሰራሽ ሀይቆች እና ፖርኮች እንዲሁም የህዝብ መፀዳጃ ቤቶች የስታዲየሙ ውጫዊ ገፀ በረከቶች ናቸው ተብሏል።
ብሔራዊ ስታዲየሙ የአለም ዋንጫን እና የኦሎምፒክን መስፈርት ያሟላ ሲሆን ስታዲየሙ ተጠናቆ ወደ ስራ ሲገባ ኢትዮጵያ አህጉር አቀፍ እና አለም አቀፍ ውድድሮችን ለማስተናገድ ትልቅ አቅም እንደሚፈጥርላት ይጠበቃል።