26/04/2026
ዘሃበሻ የዉሸት ቋት!
ከሰሞኑን በተከታታይ በቴዲ አፍሮ ዙሪያ በተከታታይነት ሰዎች ታሰሩ ምክትል ማኔጀሯ የቴዲ የቅርብ ጓደኛዉ ተወሰደ፤ ስቱድዮዉ ተሰበረ፤ ከለሊቱ 6: ሠዓት በቴዲ አፍሮ መኖሪያ ቤት ፌዴራል ፖሊሶች ሄዱ እያለ ዘገባ ሲሰራ የነበረዉ በሙሉ ዉሸት መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ በሰጠዉ መግለጫ መረዳት ተችሏል።
ይኸዉም በቴዲ አፍሮ ዙሪያ ምንም የተጀመረ ክስም እየተጣራ ያለ አንዳች ጉዳይ አለመኖሩን ፌዴራል ፖሊስ በመግለጫዉ አስታዉቋል።
"በቴዲ አፍሮ ላይ የተሰራ ምንም አይነት የወንጀል ምርመራ የለም" - ፌዴራል ፖሊስ
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ከሰሞኑ በተወዳጁ ድምፃዊ ቴዲ አፍሮ (ቴዎድሮስ ካሳሁን) ላይ እየደረሰ ነው ስለተባለው ጫና፣ ዝርፊያ እና ወከባ የቀረቡ መረጃዎች መሰረተ ቢስ መሆናቸውን በመግለጽ ማብራሪያ ሰጥቷል።
የወንጀል ምርመራ ጠቅላይ መምርያ የወንጀል ምርመራ ኦፕሬሽን ዋና መምሪያ ሃላፊ ተወካይ አቶ ሙሊሳ አብዲሳ ለቲክቫህ ኢትዮጵያ እንደገለጹት፣ ፖሊስ በአርቲስቱ ላይ የከፈተው ምንም አይነት የምርመራ መዝገብም ሆነ እያከናወነ ያለው የክትትል ስራ የለም።
አቶ ሙሊሳ በማብራሪያቸው "የፌደራል ፖሊስ እንደዚህ አይነት ውንብድና አይሰራም፤ ስብዕናውም አይደለም። የሚሰራው በህግና በህግ ብቻ ነው" ብለዋል። አርቲስቱ በአሁኑ ወቅት የፌዴራል ፖሊስ ተጠርጣሪ እንዳልሆነና በእሱ ላይ የሚከናወን ምንም አይነት ኦፕሬሽን እንደሌለ አጽንኦት ሰጥተዋል። "አርቲስቱ ቤቱ ነው ያለው፤ በስርዓት እየኖረ ነው፤ በእሱ ላይ የተደረገ ምንም አይነት ነገር የለም" ሲሉ አክለዋል።
በአርቲስቱ ላይ "ዝርፊያ ተፈጽሟል፣ የሙዚቃ መሳሪያዎቹ ተወስደዋል፣ መግለጫ እንዳይሰጥ ተከልክሏል" በሚል የሚሰራጩ መረጃዎች በሙሉ "የፈጠራ ወሬዎች" መሆናቸውን የገለጹት ሃላፊው፣ ድርጊቱን "አርቲስቱን እንደማስያዣ በመጠቀም የፖለቲካ አጀንዳ ለማራገብና ህዝብ ላይ ሽብር ለመፍጠር የሚደረግ የሳይበር ወሬ" ሲሉ ጠርተውታል።
"ይሄ ዜጋ ህገመንግስታዊ መብቱን ተጠቅሞ ሙዚቃ ሰርቷል። አርቲስት ሆኖ ሙዚቃ መስራት እና የፈለገውን አመለካከት የመያዝ ህገመንግስታዊ መብት አለው። ከዚህ ውጪ ያለ ማስረጃ ሰው የማይያዝበትን አሰራር ፈጥረናል" ብለዋል።
አቶ ሙሊሳ አብዲሳ ህዝቡ በየቀኑ የሚፈጠሩ በሺዎች የሚቆጠሩ የሀሰት ወሬዎችን ከማመን እንዲቆጠብና መረጃዎችን እንዲያመዛዝን ጥሪ አቅርበዋል። በተለይም በቴክኖሎጂ (AI) የታገዙ የሀሰት መረጃዎች ስጋት መሆናቸውን በመጠቆም፣ የጸጥታ ተቋሙ ማንኛውንም የምርመራ ስራ ሲሰራ በግልጽ ለህዝብ እንደሚያሳውቅ ገልጸዋል።
በመጨረሻም "ወንጀል የሰራ ማንም ሰው (የመንግስት አካልም ቢሆን) በህግ ይጠየቃል፤ ወንጀል ያልሰራ ሰው ግን በፍጹም አይጠየቅም" ሲሉ የፖሊስን አቋም በድጋሚ አረጋግጠዋል።