04/09/2025
ትወደው ነበር እኮ ...
ሰለሞን ይባላል። የአረቄ ምርኮኛ ነው። የሰፈሩ ሰዎች በጣም ጎበዝ አስተማሪ ነው ይላሉ። እኔ ሳውቀው ግን እንዲህ ነው....
ጠዋት ይነሳል የሙሉ አረቄ ቤት ይሰየማል። አረቄ ሳይቀምስ ማንንም አያገኝም። ጠዋቱ ፈገግ ሲል ወደረፋዱ የተዘረዘረ እንጊሊዝኛ እየቀባጠረ ይመጣል። የሚያወራበት ለዛ ከእንግሊዝኛ ይልቅ ወደ ሱማልያኛ ይሄዳል። ' Good morning ' ሲለን 'ወርያ' የሚለኝ አይነት ስሜት ነው የሚሰማኝ።
ህይወቱን ለማቆየት ብሎ የቆሻሻ ማስወገጃ መኪና ይገፋል። ከእድፋም ልብሱ ውስጥ የሚገርም የማይናቅ ግርማ ሞገስ አለው። ሁሉም ሰው እንደ ክቡር አባት ጎንበስ ቀና ብሎ ነው ሰላም የሚለው።መቆሸሹ አይታየንም።
ሰለሞን ሚስት አገኘ። ሰብለ ትባላለች። 10 አመት አረብ ሀገር ቆይታ ነው የመጣችው። በመጣች በ6 ወራት ውስጥ ቆንጆ ሰካራም ወጣት። በአጭር ጊዜ ውስጥ እንደዚህ መሆኗን አንዳንዶች አሳዛኝ ታሪክ ሰጥተዋት ሲያዝኑላት አንዳንዶች ደግሞ በራሳቸው በፈጠሩላት ታሪክ ይናደዱባታል። ግን እውነቱን ማንም የሚያውቅ አልነበረም።
ሁለቱም በስካር አለማቸው ላይ በፍቅር በየመንደሩ ሲዘዋወሩ ይውላሉ። ግን የእነሱን ፍቅር ብዙ ሰዎች አይን ላይ እንዲገባ ያደረገው አንድ ትዕይንት ነበራቸው። ብቻ በምን ምክንያት እንደሆነ አላውቅም በየመሀሉ በጥፊ ጭው አድርጎ ይለጋታል። እርሷም ዝም አትልም ...ከአቅሟ በላይ የሆነ፤ እጅ የሚቀጭ ድንጋ ተሸክማ ትዞረዋለች። ግን አትሰነዝርም ነበር።
'አያቹ ትወደኛለች' ይላል ።
'አልወድህም' እያለች ወገቡ ላይ ትጠመጠማለች።ግን አንድ ቀን...
ሰፈር ውስጥ ብዙ ሰዎች ተሰብስበው አየው። ግራ በመጋባት ሰዎቹ ወደተሰበሰቡበት አቅጣጫ አምርቼ በሰዎቹ መሀል ተሽሎክሉኬ ስገባ ...ሰለሞን ከእነግርማ ሞገሱ መሬት ተዘርሮ አየሁት። በተከፈተ አፉ ውስጥ የዝንብ መንጋ ሞልቶታል።
"ምን ሆኖ ነው ?"
"ሞቷል !"
"እኮ ምን ሆኖ ነው ?"
"ሚስቱ ፈንክታው"
"ሰብለ!?"
ለሞት ሰከንድ በቂ ነው ። ለሞት የአንድ ቀን ስህተት በቂ ነው ። ህርሟን አንድ ቀን ብትሰነዝር ፍቅሯን ገደለችው። ማንም ፍቅሯን ለማኖር የቻለችውን ዘላለም አያይም። ይህቺን አንድ ቀን እንጂ....ሰብለስ ? ሰብለስ ?
ከ6 ወራት በኃላ ሰብለ ከእስር ቤት የአእምሮ ታማሚ ናት ተብላ ተለቀቀች። ብዙዎች 'አውቃ ነው ከእስር ለማምለጥ ሀቅሏን አታውቅም እንዲሉ አሯን መብላት ጀመረች' እያሉ ያወራሉ። እርሷ ግን በዝምታ ውስጥ የድንጋይ ካብ እየሰራች አቅሟን ስታደክም ትውላለች። ሰብለ አብዳለች። ምክንያቱም ትወደው ነበር እኮ...